፩፦ መጠናናት፤
ምንም እንኳን የሰው ልጅ ተጠንቶ የማያልቅ ሳይንስ ቢሆንም ፦ ወደ ትዳር ዓለም ከመግባት በፊት ፦እንደ ሰው፥ በሰው አቅም መጠናናት እንደሚያስፈልግ ለማንም ግልጥ ነው። ይኸውም በሰከነ ልቡና ፥ በተረጋጋ መንፈስ ሊሆን ይገባል። በትውውቅ ሰሞን የተሸፈነ ብዙ ነገር ፥ በሂደት ቀስ እያለ ብቅ ማለቱ ስለማይቀር ጊዜ መስጠት ያስፈልጋል። ሰውን የምናጠናው ድካም የሌለበት ፍጹም የሆነ ሰው ለማግኘት አይደለም። ምክንያቱም እኛም ፍጹም አይደለንምና ነው ፥ አንድም በዓለመ ሥጋ ፍጹም ሰው አይገኝምና ነው። በመሆኑም፦ በእኛ ዘንድ ድካም እንዳለ ሁሉ ፦ በሌላም በኲል ድካም ሊኖር እንደሚችል አምነን ኅሊናችንን ልናዘጋጀው ይገባል። ከዚ ህ በኋላ ድካሙን ፦ በአራት ደረጃ ከፍለን ልናየው እንችላለን። ፩ኛ፦ በቶሎ የሚወገድ ድካም ፤ ፪ኛ ፦ በሂደት የሚወገድ ድካም፤ ፫ኛ፦ ልንሸከመው የሚገባን ድካም፤ ፬ኛ ፦ የማይወገድ ድካም፤
፩፥፩፦ በቶሎ የሚወገድ ድካም፤
የሰው ልጅ በትምህርት ፥ በምክርና በተግሣጽ ፦ ከጥፋቱ ሊመለስ ፥ ከድካሙም ሊበረታ ይችላል። ስለሆነም ያሉትን ደካማ ጐኖች ዘርዝሮ በማውጣት ፦ እርስ በርስ መነጋገር ፥ መማማር ያስፈልጋል። ከአቅም በላይ የሆነውን ደግሞ ወደ ካህኑ በማምጣት ማስ መከር ይገባል። እንዲህ ዓይነቱ ድካም ፦ ከእውቀት ማነስ፥ ከመካሪ ማጣት ፥ አርአያ የሚሆን ሰው ካለማግኘት በመሆኑ በቶሎ ይወ ገዳል። ጠቢቡ ሰሎሞን፦ «ምክር በሰው ልቡና እንደ ጥልቅ ውኃ ነው፤ አእምሮ ያለው ሰው ግን ይቀዳዋል።» እንዳለ፦ አእምሮ ያላቸው የሚያስተውሉ ሰዎች ይስተካከሉበታል። ምሳ ፳፥፭። «ተግሣጽን የሚወድድ ዕውቀትን ይወድዳል፤» እንዲል፦ በሁሉ ይገሠጻሉ። ምሳ ፲፪፥፩። «የተማረ ልጅ ብልህ ይሆናል፤» እንዲል፦ ልባሞች ፥ አስተዋዮች እየሆኑ ይሄዳሉ። ምሳ ፲፥፭። ይህም ከምድራዊ ሀብት የሚበልጥ ሀብት ነው። ምክንያቱም « ከብር ይልቅ ትምህርትን ፥ ከተፈተነ ወርቅም ይልቅ ዕውቀትን ተቀበሉ ፤ » ይላልና። ምሳ ፰፥፲። «ትምህርትና ተግሣጽም የሕይወት መንገድ ነውና፤» የሚልም አለ። ምሳ ፮፥፳፫።
፩፥፪፦ በሂደት የሚወገድ ድካም፤
በሰው ልጅ ሕይወት ፦ በአንድ ጀንበር ወይም በአጭር ጊዜ የማይወገድ የሥጋ ድካም አለ። አብሮ የኖረ ጠባይ እጅግ አስ ቸጋሪ ስለሆነ፦ በሂደት የሚወገድበትን መንገድ በመፈለግ በትዕግስት መጓዝን ይጠይቃል። የየዕለቱን ለውጥም መከታተል ያስፈልጋል። ዋናው ነገር ችግሩን አምኖ መቀበል ነው። እኛም በምክርና በትምህርት ድካማችንን ለማስወገድ ፥ ሕይወታችንን ለመለወጥ የሚታ ገሉትን ልናግዛቸው ያስፈልጋል። ይህ ጉዳይ ጾምና ጸሎትንም ይጠይቃል። መካሪው ክፍል «ፈጣሪ ሆይ ይህን ሰው እርዳው፤ » እያለ ፥ ድካም ያለበትም ሰው፦ « ፈጣሪዬ ሆይ፥ እርዳኝ፤ » እያለ ፦ ሊጾሙ ሊጸልዩ ይገባል። ጌታ በወንጌል፦ እንደተናገረ፦ ካልጾሙና ካልጸ ለዩ በስተቀር የማይለቅ ክፉ መንፈስ ፥ ክፉ ጠባይ አለና። ማቴ ፲፯፥፳፩።
14 фев 2015