Subscribe, Share, Like, Comment እያደረጋችሁ ላልሰሙት አሰሙ ላልነቁ አንቁ! መንፈሳዊነት ይብለጥ! የማዳመጥ ጊዜ ላይ ነን!!!
1 ዮሐ 5፥19ን ስትመለከቱ እንዲህ የሚል ታገኛላችሁ "ከእግዚአብሔር እንደሆንን ዓለም በመላው በክፉ እንደተያዘ እናውቃለን"
ከእግዚአብሔር እንደሆንን በሚለው የቀደመው ገለጻ ውስጥ 'እኛነትን' የሚወክል ጥሪ ነው ሐዋሪያው ያስተላለፈው፡፡ እኛ አለ፥ እኛ ከእግዚአብሔር የሆንን አለን፤ ደሞ በሌላው ዓለም በመላው በክፉም ተይዟል አለ፡፡ ሁለተኛው ላይ 'በመላው' የሚለው ገላጻ ደግሞ "እኛ" ብሎ ደቀመዛሙርቱና ወገኖቻቸው ከተናገሩበት የቁጥርም የስፋትም ደረጃ መብለጡን ያሳያል፡፡ ቃሉ በሌላ አነጋገር ቢገለጽ እንዲህ ሊባል ይችላል፡፡ "እኛ ከጌታ ወገን ስንሆን፤ የተቀረው መላ ዓለም ግን በክፉው ተይዟል" ሊባል ይችላል፡፡ ከእግዚአብሔር እንደሆንን ያሉት አማኞች በቁጥር ብዛትም ሆነ በርስት ስፋት ከሁለተኞቹ በመላው በክፋት ከያዙትና ከተያዙት ያንሳሉ፡፡ ስለዚህም ነው ጌታ ዮሐ. 14፥30 ላይ ዲያቢሎስን የዓለም ገዥ በማለት የገለጸው፡፡ ዓለምን በመላው በክፋት እንድትያዝ በማድረግ የርስቱን አድማስና የአባላቱን ዜጎች ለዚያውም በዛ ዘመን ተቆጣጥሮታልና ዓለምን የሚመራት ብሎታል፡፡ በዚሁ ወደ ማብቂያው ላይ ባለው ዘመንማ እንዴት ባለ ክፋት ነው የሚመራን?
+++
ዲያቢሎስ ዓለምን በመላ በክፋት የተቆጣጠረበትን የርሰት ሰፊ አድማሱን በመጠቀም "ከእግዚአብሔር እንደሆንን" የሚሉትን በአናሳ ቁጥር የሚገኙትን አማኞች ለማጥፋት ይሞክራል፡፡ በዘልማድ ቅኝት ብዙ ሰው የሚከተለው ነገር እውነት ነው ተብሎ ይወሰዳል፡፡ ባይሆን እንኳ የአብዛሃነት ጫና ስላለው ብቻ ሐሰት በብዙ ምስክሮች እውነት ትሆናለች፡፡ ይሄ ሁኔታ ታዲያ አጥፊው ጠላት በአምልኮት ክንድ ውስጥ ያሉትን በቁጥር አነሰተኛ የሆኑት አማኞች ላይ ከፍተኛ የሆነ ተጽዕኖ እንዲያሳድር ያግዘዋል፡፡
እስኪ አምልኮተ እግዚአብሔርን ከፍቅር መሠረት ላይ አንስታችሁ የገነባችሁ ሰዎች ኑሮአችሁ ምን ይላል? በየሄዳችሁበት ከሰው ጋር መግባባት አልተሳናችሁም? በየዋላችሁበት ቦታ ላይ ጆሮ ለመስጠት የሚነፍጉ ሰዎች አልበዙባችሁምን? በየአቅጣጫው ያሉት ሰዎች ስለ ስግደት ስታነሡባቸው ፊታቸውን አልከሰከሱባችሁምን? ይሄ ምንድነው ምክንያቱ ከውስጥ ያለው በጎ ያልሆነው መንፈስ ከላይ እናንተ የምታሰሙት የአምልኮት መረጃ ስለሚመረው፤ የሱን ምሬት እንደ ባለጋራነቱ ለሰውየው በማጋራት የምትናገሩት ነገር እንዳይጥመው ያደርገዋል፡፡ ለዚህ ነው ብዙ ወገኖቻችን ስለ ጸሎት ቤት፣ ስለ አምልኮት ስግደት፣ ስለ መቁጠሪያ፣ ጠላትን ስለመቃወም ሲነሣባቸው የሚጎመዝዛቸው፡፡
+++
አሁን እዚህ ጋር የመንፈሱ የአሠራር ዘዴው ምን ይሆናል፤ ብዙ ሰው ያለው ነው ትክክል በሚል የጭፍንነት ምልከታ ውስጥ ገብቶ ክፋትን አብዝቶ በማስወደድ፤ እውነት ላይ እንዲመሽባት እያደረገ ከመጀመሪያው ሰዎች የአምልኮት ትምህርት መረጃዎችን እንዳይቀበሉ በተለያዩ ሽፋኖች እየከለለ፤ እንደምንም ከእግዚአብሔር ርዳታ ጋር አልፈው መስገድ መጸለይ ሲጀምሩ ደግሞ የዓለምን የመላ የክፋት ኃይል አብዛሃነትን በመጠቀም የአማኞቹን መንፈሳዊ ሞራል፣ እሴት፣ አቅምና ተስፋ በመጉዳት የእግዚአብሔርን ጦር ዕቃ ለማስጣል ይሞክራል፡፡
4 окт 2024