Subscribe, Share, Like, Comment እያደረጋችሁ ላልሰሙት አሰሙ ላልነቁ አንቁ! መንፈሳዊነት ይብለጥ! የማዳመጥ ጊዜ ላይ ነን!!!
ቃሉን ደግመን እንመልከተው፡፡ እናስተውል ዘንድ እግዚአብሔር ይርዳን፡፡ "ዓለሙን ሁሉ የሚያስተው፥ ዲያብሎስና ሰይጣን የሚባለው ታላቁ ዘንዶ እርሱም የቀደመው እባብ ተጣለ፤ ወደ ምድር ተጣለ መላእክቱም ከእርሱ ጋር ተጣሉ።" (የዮሐንስ ራእይ 12፥9)
"ዓለሙን ሁሉ" ማለት ምን ማለት ነው? አንድ ጤነኛ ሰው ከላይ በርዕሱ የተጠቀሰውን "እያንዳንዱ ሰው መንፈስ አለበት ወይ?" የሚለውን ጥያቄ ለመመለስ እንዲችል፤ አስቀድሞ ይህን የመጽሐፍ ቅዱስ ቃል በግርድፉ እንኳን መገንዘብ አለበት፡፡ እንኪያስ "ዓለሙን ሁሉ" የሚለው ቃል ምን ይነግረናል? ዓለሙን ሁሉ ማለት ምን ማለት ነው? በዓለም አንዳንድ ቦታዎች ላይ አላለም፡፡ በዓለም አብዛኛው ሥፍራ ላይም አይልም፡፡ ዓለምን ሁሉ የሚለው እያንዳንዱን ሰው በሚነካው ቃል ውስጥ፤ ሁሉም የሰው ልጆች እንደተጠቀለሉ ሰማያዊው ቃል ቅልብጭ አድርጎ ይናገራል፡፡ ወደ ዓለም ሁሉ የመጣው ደግሞ እያንዳንዱን የአዳም ልጅ አስቶ ያጠፋው ዘንድ ነው፡፡ መኖሪያውም ታዲያ በአብዛኛው ጊዜ በሰው ልጅ ሕይወት ውስጥ ነው፡፡ ነገር ግን ይሄንን ያስተውሉ ዘንድ ያላቸው ጥቂቶች ናቸው፡፡ በቀደመው ዘመን ከጥቂቶቹ ወገን ሆነው ይህንን ያስተዋሉት የጌታ ደቀመዛሙርት እንዲህ አሉ፤ "ከእግዚአብሔር እንደ ሆንን ዓለምም_በሞላው በክፉው እንደ ተያዘ እናውቃለን።" (1ኛ የዮሐንስ መልእክት 5፥19)
አሁን ይሄን ጽሑፍ የሚያነቡ ዓይኖች ሦስት ምድብ ላይ ይገኙ ዘንድ ግድ ነው፡፡ አንደኛው ፍጹም ሥጋዊያን ዓይኖች ናቸው፡፡ እነዚህኞቹ እንዲህ አይነት መንፈሳዊ ጉዳይ በምንም ተዓምር አይጥማቸውም፡፡ በሚያነብቡት ጊዜ ከውስጥ በባሕሪይ፣ በልምድ፣ በኑሮ ውስጥ ተመሳስሎ የተቀመጠው አጥፊ መንፈስ አብሮ ስለሚያነብ፤ በነፍስ በኩል አስተውለው የእግዚአብሔር ቃል ሕይወታቸውን እንዲመረምረው ዕድል አይሰጣቸውም፡፡ ስለዚህ ወይ ጀምረው ያቋርጡታል፤ አሊያ ጨርሰው ቢያነቡት እንኳን ደረቅ የሆነ ትርክት፣ ዝም ብሎ የተደረደረ የቃላት ጋጋታ፣ ምንም ከእነርሱ ሕይወት ጋር የሚያገናኘው እንደሌለ አድርገው እንዲገነዘቡት ልቦናቸውን በጠባብ መስመር ላይ አስገብቶ ውስጣቸውን ይገዛዋል፡፡ ሁለተኛዎቹ ከሥጋዊ ወደ መንፈሳዊ ዓይንነት ለመሄድ እየጣሩ ያሉ ሰዎች ናቸው፡፡ እነዚህኛዎቹ በከፊል ይረዳሉ፤ በከፊል አይረዱም፡፡ በሕይወታቸው፣ በጊዜያቸው፣ በአኗኗራቸው፣ በዕድላቸው፣ በቤታቸው ውስጥ ያለውን ጠላት ተገንዘበው እንዲህ አይነት መረጃ ለማግኘት በጣም የሚጓጉ ናቸው፡፡ ነገር ግን ትልቁ ችግር አንድ እግራቸው ዓለም ውስጥ፤ አንድ እግራቸው መንፈሳዊ እውነት ውስጥ ስለሆነ፤ በመረዳትና ባለመረዳት መካከል እንደጊዜው ከጊዜው ጋር የሚለዋወጡ ይሆናሉ፡፡ ሦስተኛዎቹ የዓለም መናኞች መንፈሳዊ ዓይን ያላቸው ሰዎች ናቸው፡፡ እነዚህ፤ የምድር ኑሮ የጊዜ ቆይታ ብቻ እንደሆነ የተረዱ፤ እያንዳንዷ ሰኮንዳቸው ሰማያዊ እውነትን እንድትረከብ የሚጥሩ፤ የክፉ መናፍስትን አሠራርና ስውር አካሄድ በሕይወታቸው ውስጥ የተገነዘቡ፤ የእግዚአብሔርን መለኮታዊ እውነትና ኃይል በምግባር ለመያዝ በየቀኑ የሚታትሩ እና የመጽሐፍ ቅዱስን የኑሮ ቅርጽ በእነርሱ ኑሮ ውስጥ አዛምደው የሚያስተውሉት ናቸው፡፡ እያንዳንዷ በእንዲህ አይነት መረጃ ውሰጥ የሚጣሉትን ቃላት በነፍሳቸው ሆነው ያነቡታልና የመኖር መሠረታዊ ትርጉም በደንብ የገባቸው በየቀኑ የሚማሩ ሰዎች ናቸው፡፡ ስለዚህም መንፈስ ቅዱስ እንደ አንባቢው ውስጣዊ ቅንነትና እውነትን የመረዳት አቅም፤ በደረጃው ልክና ጊዜው በሆነለት ልክ ሰማያዊ ቃልን ለሥጋና ለነፍሱ ይገልጥለታል፡፡
የሰው ልጅ በምድር የዕድሜ ቆይታው ሲመላለስ የመኖሩ መሠረታዊ ትርጉም ምንድነው? ሐብታም መሆን ነው? ባለዝና መሆን? በእውቀት ማዕረግ ከፍ ማለት ነው? ባለሥልጣን መሆን ነው? እነዚህና መሰል ዓለማዊ ጉዳዮችን በስኬት መያዝና ማጠናቀቅ ደግሞ የከንቱ ከንቱ እንደሆነ መጽሐፍ ቅዱስ አስምሮ ይነግረናል፡፡ " ሰው ዓለምን ሁሉ ቢያተርፍ ነፍሱንም ቢያጐድል ምን ይጠቅመዋል?" (የማርቆስ ወንጌል 8፥36)
3 ноя 2020