#Subscribe_Share_like_በማድረግ_አገልግሎቱን_ይደግፉ።
በተለይ በዚህ በዲያቢሎስ ዘመን፤ የቤተ እግዚአብሔር መምህራን ሳይቀሩ ጥላቻን ያስተላልፋሉ፡፡ ስድብ የሚያሰለጥኑ፣ መለያየትን የሚያውጁ፣ ክፋትን የሚያበለጽጉ፣ በቀልን የሚያለማምዱ፣ መካሰስን የሚያስተምሩ፣ ለደግነት ስም የሚሰጡ፣ የሰው ችግር በጭራሽ የማይቸግራቸው፣ ሲሆንም ሰውን መጉዳት ትክክል እንደሆነ የሚያስቡ እልፍ ሰዎች አሉ፡፡ እነዚህን ሰዎች በጣም በሚገርም ሁኔታ መራቅ አስቸጋሪ ይሆንብናል፡፡ ለምንድነው ይሄ፤ ከውስጥ በኩል ያለ የመናፍስት አንድነት ስላለ ነው፡፡ በአምልኮተ እግዚአብሔር ውጊያ የደከመ መንፈስና ምኑም ያልተነካ መንፈስ ሲገናኙ ለክፋት መተባበር ይቸገራሉ፡፡ ነገር ግን፤ ሁለት የማይሰግዱ፣ የማይጸልዩ፣ የማይቀደሱ፣ የአጥፊ መንፈሶችን የጥፋት ስልት የማያውቁ ወገኖች ሲገናኙ፤ መንፈሶቻቸው በጣም በቀላሉ ተደራጅተው ለጥፋት አንድነት ይሰለፋሉ፡፡ በዚህ ጊዜ ሰዎቹ ከነአካቴው ባይተዋወቁ እንኳን ክፉ ነገር ለመፈጸም፣ ለመሳደብ፣ ለማማት፣ በጋራ ለመጥላት፣ በአንድነት ለማጥቃት ይተዋወቃሉ፡፡ እናስተውል፡፡ እንኳን የማይተዋወቁ፥ የሚተዋወቁም ሰዎች አንድ ላይ ደግ ለማድረግ የሚችገሩ ሆነው፤ ለማጥፋት ግን በቀላሉ የሚተጋገዙት ውስጥ ካሉት የመናፍስት ሕብረት ጋር በተያያዘ ምክንያት ነው፡፡ በመሆኑም፤ በተቻለ አቅም ይህንን የመናፍስት አንድነት ለመስበርና በምትኩ የመንፈስ ቅዱስ አንድነትን ለማምጣት፤ መናፍስትን ዘወትር በማድከም ልምምድ ውስጥ እየተገኙ፤ ስለ ፍቅር ቦታ የሚሰጡ ሰዎችን የሕይወት አርአያ በማድረግ ኑሮን በቀና መስመር ላይ ለማሳረፍ ጉልበት ማውጣት ያስፈልጋል፡፡
30 сен 2024