እስከዛሬ በመጣንበት የሕይወት ምዕራፎች ውስጥ በተጓዝነው ጉዞ መነሻና መካከል ላይ ኑሮአችን ምን ይመስላል? የእኛና የቤተሰብ ዘመድ አዝማዶቻችን ጤና የተጠበቀ ነው? ሰላማችን የጸና ነው? በረከታችን እያደገ የሚሄድ ነው? ጊዜያችን ትርፋማ ነው? ሥራችን ውጤታማ ነው? ትምህርታችን ፍሬያማ ነው? ትዳራችን በጸጋና በደስታ የተሞላ ነው? ቤታችን በፍጹም ሰላምና እፎይታ የተጎበኘ ነው? ከቤተሰቦቻችን፣ ከዘመዶቻችን፣ ከትዳር አጋሮቻችን፣ ከወዳጆቻችን፣ ከባልደረቦቻችን ጋር ያለን ግንኙነት እንዴት ያለ ነው? ሰላማዊ ነው? ፍቅር አለበት? ደስታ ይታይበታል? ተስፋና ራእይ የሚባሉ ሰማያዊ ምሪቶች ለሕይወታችን ቀጣይ አቅጣጫ መሪ ሆነውልን ያውቃሉ? በእምነታችን አካሄድ ውስጥ በጸጋ ጥላ ውስጥ ተጥልለን እናውቃለን? በሃይማኖታችን እውነታ ውስጥ የሚታይ መንፈሳዊ ትሩፋትና ዋጋ አለን? እንዴት ነው እስኪ እስከ አሁን የመጣንበት የሕይወት ምዕራፍችን ገጽታ?
ሕይወት ጥንድ ናት፡፡ ብርሃን ካለ ጨለማ አለ፡፡ ከፍታ ካለ ዝቅታ አለ፡፡ ፍቅር ካለ ጥላቻ አለ፡፡ ቀኝ ካለ ግራ አለ፡፡ ደስታ ካለ ሐዘን አለ፡፡ ሰላም ካለ ነውጥም አለ፡፡ ክፉ ካለ ደግ አለ፡፡ ማግኘት ካለ ማጣትም አለ፡፡ ይሄ እውነት ለምድር እንደ ተፈጥሮ ሕግ ሆኗል፡፡ ስለዚህ በየጊዜያቱ በጎና ክፉን በጣምራ ማስተናገዳችን የሰውነት ሕልውናና የዓለም አካሄድ ነው፡፡
ታዲያ ሁላችንም አኗኗራችንን መለስ ብለን አጢነን በምንፈትሽበት ጊዜ፤ 'በየትኛው የሕይወት ገጽታ ላይ ነው ብዙ እየቆየን ያለነው? የትኛው የኑሮ መልክ ላይ ነው ጊዜያችን እየጠፋ ያለው? አብዝተን እያስተናገድን ያለነው የትኛውን የሕይወት ክፍል ነው?' ብለን መመርመር ስንጀምር፤ ኢትዮጵያውያን እንደ ተናጠልም ሆነ እንደጋራ ጊዜና ሰማያዊ እውነት ከዘመን ዘመን፥ ከትውልድ ትውልድ፥ ወደፊት በሄድን ቁጥር፤ በአንደኛው ግራ ዘመም ጎን ላይ እየተገኘን ለመከራ የተፈጠርን እስኪመስል ድረስ ብዙ የብዙ ስቃዮች እየተጋረጡብን እንደሆነ ከነባራዊ ኑሮአችን ሌላ ምንም ተጨባጭ ማስረጃ አይኖርም፡፡
እስኪ ሰክነን እናምሰልስለው፡፡ ለምን በአገራችን ውስጥ ጥላቻ፣ ጎጠኝነት፣ ስደት፣ ድህነት፣ ምቀኝነት፣ ተንኮለኝነት፣ ነገረኝነት፣ ጠበኝነት፣ ሌብነት፣ ሙሰኝነት፣ መለያየት፣ መጨካከን፣ መተረማመስ፣ ግራ መጋባት፣ መፍትሔ ማጣት ከጊዜ ጊዜ በጣም እየጨመረ ይሄዳል? ሐዘን ወደ ደስታ ሊመራን ነበረ የሚገባው፡፡ እኛ በሐዘናችን ውስጥ ለረጅም ጊዜ ሆነን ደስተኛ እንደነበርን ነው የምናስታውሰው፡፡ በጊዜያት ሂደት ውስጥ በዓይናችን እያየን ሰዎች ወደ አውሬነት እየተቀየሩ ብዙ ሰቅጣጭ ዜናዎችን የምንሰማበት ድግምግሞሽ እያሻቀበ እያሻቀበ መጣ፡፡ የዚህ ምክንያቱ ምንድነው?
ምክንያቱ፤ እንደ ትውልድ፥ ትውልድ ሆነው በእያንዳንዳችን ቤትና ቤተሰብ መዋቅር ውስጥ ተሰውረው የገቡት የዲያቢሎስ ሠራዊቶች ባላጋራ ሆነው፤ ሕይወታችንን፣ ዕድሜያችንን፣ አካሄዳችንን፣ ባሕሪያችንን፣ ልማዳችንን፣ ዕውቀታችንን፣ ሥራችንን፣ አኗኗራችንን፣ ፍላጎታችንን፣ እቅዳችንን እና ራእያችንን ተጋርተው ከፊት እየቀደሙ መሪ በመሆን በፍቃዳቸው ቦታና ጊዜ ላይ ስለሚያውሉን ነው፡፡
"ለአብ፣ ለወልድ፣ ለመንፈስ ቅዱስ እሰግዳለሁ" የሚለውን የአምላክ የዘወትር ስግደት ስንረሳ፤ በመጀመሪያ ከልብና ከሰውነታችን ውስጥ እግዚአብሔር የሌለ እስኪመስል ድረስ ፍጹም ተረሳ፡፡ በሁለተኛው ከውስጥ የረሳንበት ገጽታ ወደ ውጪም ያንኑ ሲገልጠው፤ ኑሮአችን እግዚአብሔርን ረሳ፡፡ በቃ ከዚህ በኋላ እግዚአብሔር በሌለበት ቦታ ላይ የጀመርነው የሕይወት ጉዞ መካከሉ ላይ እንቅፋት እየበዛበት፤ ማብቂያውም ከጠበቅነው እቅድና ግብ እየሳተ የሚያሳዝነን እየሆነ፤ በሮጥንበት አቅጣጫ መድረሻ ላይ በአብዛኛው ድካም ብቻ እያተረፍን፤ ነገ ለሚጎድለው ቀን ዛሬ ሙሉ የሆነ ነገርን ለማስቀመጥ እረፍት አጥተን ሰላም አጥተን እንባዝናለን፡፡ እስከ መቼ ነው በእውነት እንደዚህ የምንኖረው?
Subscribe, Share like በማድረግ አገልግሎቱን ይደግፉ።
22 ноя 2020