በርባንና ክርስቶስ ዛሬም ግራና ቀኝ ቆመዋል፡፡ እናስተውለው ዘንድ የሚያስፈልገው ነገር፤ ይሄ ምርጫ ዘወትር በየቀኑ እንደየሕይወታችን አጋጣሚ መቅረቡን ይቀጥላል፡፡ ሰላም ሰጪነትን እና ሰላም ነጣቂነትን የሚወስኑ ሁነቶች በየቀኑ ምርጫ ሆነው አሉ፡፡ መታገስ እና አለመታገስን የሚፈትኑ ነገራት ዘወትር አሉ፡፡ ቁርጠኝነትን አሊያ ግዴየለሽነትን የሚያስመርጥ አጋጣሚ በየዕለቱ ወደኛ ይመጣል፡፡ ይቅርታ ማድረግ እና በደልን መመዝገብ አሁንም ምርጫችን ነው፡፡ ቸርነትና ንፉግነት በየኑሮአችን መስመር ላይ ተራርቀው ቆመው መልሳችንን ይጠብቃሉ፡፡ ስለዚህ እንወስን፡፡ ማንን መርጠናል? በርባንን ነው ክርስቶስን?
ልብ እንበል! ዓለም፤ የምርጫ ኮሮጆዋን ለበርባን ከሰጠች ቆይታለች፡፡ ያኔ በዘመነ ክርስቶስ፤ የበዙት ሰዎች ስለ በርባን እንደጮኹ ሁሉ፤ ዛሬም ይኸው ጊዜ ራሱን ሲደግም ብዙ ሰዎች ወደ ተገለጠው በርባን ይጮኹ ዘንድ ውስጣቸው ያለው ያልተገለጠው በርባንን ጥፋትን፣ ግፍን፣ አመፃን፣ ስግብግብነትን፣ ትምክህትን፣ ግንፍልተኝነትን፣ ቸልተኝነትን፤ እየመራ፥ የብዙሃን ድምፅ የአንድነት ፍላጎት ሆኗል፡፡
እንኪያስ፥ ምርጫችን ክርስቶስ ከሆነ ዘንዳ፤ ከውስጥ ካለው በርባን ጋር በየሰኮንዱ ልንታገል ግድ እንደሚያስፈልገን እናስተውል፡፡ 'የዓለም መናኝ' ሆኖ ለመኖር በመጀመሪያ ከውስጥ ያለው በርባን በየቀኑ መታሰሩን ማረጋገጥ ግድ ነው፡፡ አለበዚያ ሁለት ዛፍ በአንዴ እንወጣ ስንል፤ መድረሻ ማረፊያችን የሚሆነው ሁለቱንም ዛፍ አለመውጣት ነው፡፡ ሁለቱንም አለመውጣት ሆነ የግራው ዛፍ ላይ መገኘት ደግሞ የውስጠኛው በርባን ፍላጎት ነው፡፡ "በራድ ወይም ትኩስ እንዳይደለህ ሥራህን አውቃለሁ። በራድ ወይም ትኩስ ብትሆንስ መልካም በሆነ ነበር። እንዲሁ ለብ ስላልህ በራድም ወይም ትኩስ ስላልሆንህ ከአፌ ልተፋህ ነው።" (የዮሐንስ ራእይ ምዕ. 3፥5-6)
29 сен 2024