መላእክት የእግዚአብሔር ልጆች ተብለው ተጠርተዋል (ኢዮብ 1፥6፤ 2፥1፤ 38፥7)። የዕብራውያን ጸሓፊ ግን ከመላእክት መካከል እግዚአብሔር ማንንም ልጄ በማለት እንዳልጠራና አባትም ሊሆናቸው ቃል እንዳልገባ ይናገራል (1፥5-6)። ስለዚህ መላእክት የእግዚአብሔር ልጆች የሆኑበትና ኢየሱስ የእግዚአብሔር ልጅ የተባለበት ልጅነት አንድ ዐይነት አይደሉም ማለት ነው። በአንድ በኩል፣ “እስራኤል የበኵር ልጄ ነው” በማለት ስለ ተጻፈ የእስራኤልን የበኵር ልጅነት እናውቃለን (ዘፀ. 4፥22፤ ኤር. 31፥9)። ነገር ግን መላእክት የተፈጠሩት ከእስራኤል መመረጥ በፊት ነው። ታዲያ መላእክት ቀድመው ተፈጥረው፣ እንዴት እስራኤል የበኵር ልጅ ልትሆን ትችላለች? በሌላ በኩል ደግሞ፣ ኢየሱስ የእግዚአብሔር በኵር መሆኑን መጽሐፍ ይመሰክራል፤ “ልጁ በብዙ ወንድሞች መካከል በኵር ይሆን ዘንድ …” የተባለው ስለ እርሱ ነውና (ሮሜ 8፥29፤ ዕብ. 1፥6)። ታዲያ እስራኤል በኵር ሆና፣ ኢየሱስም እንዴት በኵር ይሆናል? ይህም የተለያየ ዐይነት የእግዚአብሔር ልጅነት ስለ መኖሩ ተጨማሪ ማስረጃ ነው።
አይሁድ ከጌታ ኢየሱስ ጋር በሚከራከሩበት ወቅት፣ “አንድ አባት አለን፤ እርሱም እግዚአብሔር ነው” በማለት ተናግረዋል (ዮሐ. 8፥41)። ኢየሱስ “እግዚአብሔር አባቴ ነው” ሲል ግን ራሱን ከእግዚአብሔር ጋር እኩል እንዳደረገ ገብቷቸው ሊገድሉት ወስነዋል (ዮሐ. 5፥18፤ 19፥7)። ለምን? ምክንያቱም የእግዚአብሔር ልጅነት ሁሉ አንድ ዐይነት አይደለም።
በዚህም ላይ መጽሐፍ ቅዱስ፣ ኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሔር አንድያ (ብቸኛ) ልጅ መሆኑን እየነገረን፣ በእርሱ የሚያምኑ ሁሉ የእግዚአብሔር ልጅነትን እንደሚያገኙ ጨምሮ ያስተምረናል። ስለዚህ የተለያየ ዐይነት የእግዚአብሔር ልጅነት መኖሩን መቀበል ይኖርብናል።
17 окт 2024