ዐገር አከል የአገር ልሳን
ጥላሁን ገሰሰ ካለፈ እነሆ 8 አመታት ተቆጠሩ፡፡ ይህ ታላቅ ሰው በሞት በተለየበት የሚያዝያ ወር እርሱን የሚዘክር ዝግጅት ተሰናዳ ሲባል ባለመስማቴ እጅጉን አዝናለሁ፡፡
ጋሽ ጥላሁን በልቤ ብራና ላይ በርካታ ውብ ቁምነገሮችን ቢጽፍም፣ ዛሬ ግን በድምጹ እውስጤ የከተባትን፣ ከነፍሴ ጋር በውበት ያዋሃዳትን ኢትዮጲያን እተርካለሁ፡፡ ጋሽ ጥላሁን ኢትዮጲያን በምን በምን መልክ እንደነገረኝ አወጋለሁ፡፡ ጥላሁን በጥኡም ልሳኑ ያዜማትን መልከብዙ፣ ፈርጀብዙ ኢትዮጲያ አወሳለሁ፡፡ እርሱም፣ ድምጹን ሞት እንዳይረታው አድርጎ ሁሌም ስለምትኖረዋ አገሬ አቀንቅኖልኛልና ባለበት የማያልቅ ምስጋና ይድረሰው፡፡
ኢትዮጲያ እኔ ልብ ውስጥ የተጻፈችው በአይነትም በቁጥርም ብዙ በሆኑ ብእሮች ነው፡፡ ለዚህ ነው በሀሳቤና በደሜ ዘውትር የምትዘዋወረው፡፡ በእኔ አእምሮ ኢትዮጲያ ከአለም ትሰፋለች፡፡ ከሁሉ ትበልጣለች፡፡ ይህችን ውብ ማንነትና ስሜት ከሰሩልኝ አላባዎች አንዱም የጥላሁን ገሰሰ ድምጽ ነው፡፡ ለነገሩ እርሱም ቢሆን ኋላ የነገሰበትን መድረክ የባረከው የኢዩኤል ዮሀንስ ስራ በሆነው
ጥላ ከለላ ዬ ኢትዮጲያ ሀገሬ፣
ኩራት ይሰማኛል ካንቺ መፈጠሬ
በሚለው ዘፈን ነው፡፡ እውነት ነው፡፡ እስከህይወቱ ፍጻሜ ባንዲራዋን እንደዘፈነም እንደለበሰም፣ ከቤተመንግስት እስከአገሪቱ ዳር ድንበሮች በነበሩ መድረኮች ላይ ሲያበራ ኖሮ ነው ያለፈው ጥላሁን፡፡
ኢትዮጲያ ከአለም ትሰፋለች፡፡
ኢትዮጲያ ሁልጊዜም በክብር ትኑር፡፡
30 апр 2017